የሰነድ ማረጋገጫንና የምዝገባ አገልግሎትን ዲጂታላይዝድ በማድረግ ተገልጋዩን ከእንግልት ለማስቀረት እየተሰራ መሆኑን የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ዋና አፈ-ጉባኤ ወይዘሮ አስካለች አልቦሮ አስታወቁ።
የክልሉ ፍትህ ቢሮ DARS ቴክኖሎጂ የኦንላይን አገልግሎትን በይፋ አስጀምሯል።
በማስጀመሪያ መርሐ ግብሩ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ዋና አፈ-ጉባኤ ወይዘሮ አስካለች አልቦሮ እንዳሉት በክልሉ ሲሰጥ የቆየው የሰነድ ማረጋገጥ አገልግሎት ደህንነቱን ባልጠበቀ መልኩ ሲስራ መቆየቱን አስታውሰዋል።
ሆኖም የሰነድ ማረጋገጥና የምዝገባ አገልግሎት ዘመኑን በዋጀ ዲጂታላይዝ በማድረግ ተገልጋዩን ከእንግልት ለማስቀረት እየተሰራ ስለመሆኑን ወይዘሮ አስካል ተናግረዋል።
ለስኬታማነቱም የባለሙያዎች የአቅም ግንባታ ስልጠና እንዲሁም ግብዓት በማሟላት የክትትልና ድጋፍ ስራዎች መስራታቸውንም አፈ ጉባኤዋ ጠቁመዋል።
የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ፍትህ ቢሮ ኃላፊ አቶ መሃመድ ሀሚድ በሰነድ ማረጋገጥና ምዝገባ አገልግሎት ላይ የሚስተዋለውን እንግልትና የአሰራር ችግር ለመቅረፍ DARS ቴክኖሎጂ የኦንላይን አገልግሎትን በይፋ መጀመሩን ተናግረዋል።
የኢፌዴሪ ሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር አቶ ሀሚድ ኪኒሶ ቀልጣፋ፣ ተዓማኒነቱና ድህነቱ የተረጋገጠ ዲጂታል ኢትዮጵያን ለመገንባት ቴክኖሎጂው አይነተኛ ጠቀሜታ እንዳለው ተናግረዋል።
የሀገሪቱ የመረጃ ስርዓት በአንድ ማዕከል መሆኑ ደግሞ ለተለያዩ አገልግሎቶች መሳለጥ ሚናው የጎላ ነው ብለዋል አቶ ሀሚድ።
ተደራሽነቱ ላይም በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ ዳይሬክተሩ አስገንዝበዋል።
የተቋሙ ሰራተኞች እና የአገልግሎቱ ተጠቃሚዎች በበኩላቸው ቴክኖሎጂው ሀሰተኛ መረጃን ከማስቀረት ባሻገር ቀልጣፋ፣ ምቹ ጊዜና ጉልበት ቆጣቢ በመሆኑ በሌሎች ተቋማትም መተግበር እንዳለበት ተናግረዋል።
የሰነድ ማረጋገጥና ምዝገባ ኦንላይን አገልግሎት ማስጀመሪያ ላይ ድጋፍ ላደረጉ ተቋማት ምስጋናና ሰርተፊኬት መስጠቱን የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ሚዲያ ዘግቧል።
