
(አሶሳ፣ ኅዳር 26/2018 ዓ/ም) ሙስናን የሚጸየፍ ትውልድ በመገንባት የኢትዮጵያን ብልጽግና ማረጋገጥ የሁሉም ድርሻ ሊሆን እንደሚገባ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ ወ/ሮ አስካለች አልቦሮ ገለጹ።
በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል “ትውልድን በስነ-ምግባር፣ ተቋምን በአሰራር” በሚል መሪ ቃል በዓለማቀፍ ደረጃ 22ኛው፣ በኢትዮጵያ ደግሞ 21ኛው የጸረ-ሙስና ቀን በክልል ደረጃ ዛሬ በፓናል ውይይት ተከብሯል።
በመድረኩ የተገኙት የክልሉ ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ ወ/ሮ አስካለች አልቦሮ፣ የሀገርን ብልጽግና ለማረጋገጥ ሙስናን የሚጸየፍ ትውልድ መገንባት ወሳኝ ተግባር ነው ብለዋል።
ለዚህም ትውልዱን ከታች ጀምሮ በስነ-ምግባር ማነጽ የሁሉም ድርሻ መሆኑን ተናግረዋል።
የመንግሥት ተቋማት ተጋልጋዮችን ከማጉላላት እና ከእጅ መንሻ የጸዳ አገልግሎት መስጠት የሚያስችል አሰራር ዘርግተው ሊሰሩ እንደሚገባ አስረድተዋል።
በኢትዮጵያ የብልጽግና ጉዞ ውስጥ ሙስናን ሙስናና ብልሹ አሰራርን ከመጸየፍ ባለፈ ተግባሩን ማጋለጥ እና ተገቢ እርምጃ መውሰድ እንደሚገባም ወ/ሮ አስካለች ገልጸዋል።
የክልሉ ስነ-ምግባር እና ጸረ-ሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር ከማል ሀሰን፣ ሙስና በዓለማቀፍ ደረጃ ልማት እና ብልጽግና እንዳይረጋገጥ ቀደሚ ስጋት መሆኑን አንስተዋል።
ሙስናና ብልሹ አሰራር የሚፈጸምበት መንገድ ውስብስብ እና ድብቅ በመሆኑ በአንድ ተቋም ብቻ ለውጥ ማምጣት አስቸጋሪ ነው ያሉት ኮሚሽነሩ፣ በጸረ-ሙስና ትግል ውስጥ ሁሉም በትኩረት ሊሰራ ይገባል ብለዋል።
የጸረ-ሙስና ቀንን ከማክበር ባለፈ ትውልድን በስነ-ምግባር ለማነጽ እና የተቋማትን አገልግሎት በማሻሻል ተጨባጭ ውጤት ለማምጣት ባለድርሻ አካላት የበኩላቸውን እንዲወጡ ጥሪ አቅርበዋል።
#የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የመንግሥት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ
