በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የ2018 በጀት ዓመት የመጀመሪያ ሩብ ዓመት ዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ በመካሄድ ላይ ነው፡፡
የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻድሊ ሀሰን በመድረኩ ማስጀመሪያ፤ በ2018 የበጀት ዓመት ሕዝብን ተጠቃሚ የሚያደርጉ የልማትና የመልካም አስተዳድር ዕቅዶች ላይ ትኩረት ተደርጎ እየተሠራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
በመጀመሪያ ሩብ ዓመት በመኸር እርሻ፣ በማዕድን፣ በክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት፣ በንቅናቄ ሥራዎች የተሻለ አፈጻጸም መመዝገቡንም ርዕሰ መስተዳድሩ ጠቁመዋል፡፡
የአፈጻጸም ግምገማው በመጀመሪያው ሩብ ዓመት የታዩ ጥሩ አፈጻጸሞችን በላቀ ሁኔታ ለማስቀጠል፣ ውስንነቶችን ለማረም እና በቀጣይ ለሚከናወኑ ተግባራት አቅጣጫ ለማስቀመጥ የሚያግዝ መሆኑን ርዕሰ መስተዳድሩ ገልፀዋል፡፡
የክልሉ ፕላንና ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ቃሲም ኢብራሂም፣ ክልሉ በበጀት ዓመቱ የተለዩ 12 ዋና ዋና የትኩረት መስኮችን ለመፈጸም እየሠራ መሆኑን ጠቁመው፣ በመጀመሪያው ሩብ ዓመት በተለያዩ ዘርፎች አበረታች አፈጻጸም መመዝገቡን አብራርተዋል፡፡
የክልሉ የአስፈጻሚ አካላት የመጀመሪያ ሩብ ዓመት የዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻድሊ ሀሰንን ጨምሮ የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች በተገኙበት እየተካሄደ ነው።

